-> በአንድ ጫካ ውስጥ አንድ ከሺ ዓመታት በላይ እድሜ የጠገበ ዋርካ ነበረ፡፡ ዋርካው እጅግ ሰፊ፣ ውስብስብና ታላቅ ነው፡፡ በላዩ ላይ አዕዋፍ፣ በሥሩም እንስሳት ይጠለሉ ነበር፡፡ ከፊሉ ፍሬውን ከፊሉም ቅጠሉን ይመገባሉ፡፡
ሌሎቹም ግንዱንና ሥሩን ፍቀው ይበላሉ፡፡ አንዳቸው ለሌላቸው እንስሳትና አዕዋፍ የጠቀሙበት፣ አንዳቸውም
አንዳቸውን የበሉበት ዘመን ነበር፡፡ አንዳቸው ከአንዳቸው ጋር የሚጋቡበት፣ አንዳቸውም ከሌላቸው ጋር
የሚዋጉበት ዘመን አለ፡፡ ፈረስና አሞራ ተጋብቶ ክንፍ ያለው ፈረስ ተወልዶ ነበር አሉ፡፡ ታላላቆቹ እንስሳት
በልተዋቸው ዘራቸው የጠፉ እንስሳትም አሉ፡፡
እነዚህ እንስሳት አለመግባባታቸው እየጨመረ መጥቷል፡፡ አንዳንዶቹ ወፍነት፣ አንበሳነት፣ ዝሆንነት፣ ድመትነት
የሚባል ማንነት እንጂ እንስሳነት የሚባል ማንነት የለም ይላሉ፡፡ ሌሎቹ ደግሞ እንስሳነት የሚባል ማንነት እንጂ
ወፍነት ወይም በግነት፣ ፍየልነት ወይም ጦጣነት የሚባል ማንነት የለም ብለዋል፡፡ ከዚህ የተረፉት ደግሞ ሁለቱም
አለ ይላሉ፡፤ እስካሁን ግን በአንዱም አልተስማሙም፡፡
ከዋርካው ሥር የሚያርፉት እንስሳት የዋርካው ቅርንጫፎች መቆረጥ አለባቸው የሚል አቋም ይዘዋል፡፡ ለምን?
ሲባሉ እነዚህ ጨቋኝ አዕዋፍ በኛ ላይ ሲዘባነኑ፣ ኩሳቸውን ሲጥሉ፣ ከዚያም አልፈው ከላይ ሆነው እኛን ሲረግጡ
የነበረው በቅርንጫፉ ላይ ሆነው ነው፤ የቅርንጫፉ መኖር ግፍና መከራውን፣ ጭቆናና ስቃዩን ስለሚያስታውሰን
መቆረጥ አለበት ባይ ናቸው፡፡
ሌሎቹ ደግሞ በዋርካው ሥር ላይ ቂምና ትችት አላቸው፡፡ ይኼ ዋርካ አንድ ቦታ ተተክሎ የቀረው፣ ከመስፋትና
ከመደርጀት አልፎ ተራማጅ ያልሆነው፣ ሥሩ ከምድር ጋር ተክሎ ስለተያያዘ ነው፡፡ ሥሩ ባይዘው ኖሮ ስንፈልግ
አውሮፓ ወስደን የበረዶ ዛፍ፣ ስንፈልግ ካልሃሪ ወስደን የበረሃ ዛፍ ማድረግ እንችል ነበር፡፡ ሥሩ ቸክሎታል፡፡ስለዚህ ሥሩ መነቀል አለበት ይላሉ፡፡
ሦስተኛዎቹ ወገኖችም እኛ ስለቅጠሉ እንጂ ስለ ፍሬው የሚያገባን ነገር የለም ብለዋል፡፡ እነዚህ ቅጠል በል የሆኑት
እንስሳት በዋርካው ላይ ብቅ የሚሉትን ቅጠሎች ሁሉ እየቀነጠቡ ለመጨረስ በሩጫ ላይ ናቸው፡፡ እነዚህን
ወገኖች ፍሬ በል የሆኑ እንስሳት ተቃውመዋቸዋል፡፡ ቅጠሉ ከሌለ ፍሬው አይገኝም፡፡ ዋካው እንዲያፈራ ቅጠሉን
ተውለት የሚል ክርክር አላቸው፡፡ እነዚያኞቹ ግን ስለ እናንተ የማሰብ ግዴታ የለብንም፡፡ እኛ ማሰብ
የሚጠበቅብን ስለ ቅጠሉ ብቻ ነው ብለው ዘግተዋል፡፡
እነዚህ ቅጠል በል እንስሳት ስለ ሌላው የዋርካው ክፍል አይመለከተንም ባይ ናቸው፡፡ ለእኛ ጉዳዩ የቅጠል ጉዳይ
እንጂ የዋርካ ጉዳይ አይደለም፡፡ ይህንን ብለው ቅጠሎችን በሚያማምሩ ባለ ቀለም ላስቲኮች ሸፈኗቸው፡፡
ይህ ጉዳይ ደግሞ የዋርካውን ሕይወት ማሳጠር ብቻ ሳይሆን የሌሎችን እንስሳት የመኖር ሕልውናም አደጋ ላይ
ጣለው፡፡ ቅጠሉ ከተሸፈነ ይወይባል፣ አየርና ፀሐይ ወስዶ ለዋርካው ምግብ የሚሠራም አይኖርም፡፡ ዋርካውም
ሕይወቱ በጭንቅ ሆነ፡፡ ቅጠል በሎቹ ለቅጠሎች የሠሩት ጌጥ እንደ መቃብር ላይ ጌጥ ሆነ፡፡
ሌሎች ደግሞ መጡ፡፡ ይህንን ዛፍ ዋርካ ብለን መጥራት፣ ግንዱንም፣ ቅርንጫፉንም፣ ቅርፊቱንም፣ ቅጠሉንም፣
ፍሬውንም በአንድ ዋርካ ስም መጥራት የለብንም አሉ፡፡ የዚህ ዋርካ ታሪክ የመቶ ዓመት ታሪክ ነው፡፡
የቅርብ ቀን አስተያየቶች :
abebe
1679 days ago
test